Tuesday, July 31, 2012

ሰበር ዜና ! የጅዳ ቆንስል ግቢ የውሃ ገንዳ ሰው በላ !

   ኢትዮጵያዊቷ ሞታ ተገኘች !

 ይህች ኢትዮጵያዊ ሞታ የተገኘች ው በጅዳ ቆንስል ኢንባሲ ግቢ ውስጥ በገኘው የውሃ ገንዳ ውስጥ ሲሆን ወቅቱም  በግምት 3፡15 ሌሊት አካባቢ መሆኑን ለማዎቅ ችያለሁ፡፡ የዚህች እህት ሞታ መገኘት እንደሰሙ ምክትል ቆንስል ሸሪፍ በቦታው በመገኘት የአደጋ ጊዜ ፈጥኖ ደራሽ ፖሊስ ሬሳውን ከጉድጓድ አውጥተው ነብሷ ከስጋዋ ያልተለየውን  እህት ለማዳን ሲታገሉ የአይን ምስክር ነበሩ፡፡ ሆኖም ሙከራቸው ሁሉ ያልተሳካላቸው የቀይ ጨረቃ ሃኪሞች የተቻለ እርዳታ ለማድረግ ወደ ሆስፒታል በአፋጣኝ እንደወሰዷትና አምባሳደር መርዋን በድሪም ሬሳው ወደ አንቡላን ሲገባ መደረሳቸውን ለመረዳት ችያለሁ፡፡
 በጅዳ ቆንስል ኢንባሲ ግቢ ውስጥ በገኘው የውሃ ገንዳ
   በቦታው ለመገኘት እንደታዘብኩት በወቅቱ የነበሩት መርማሪዎች እጅና እግሯ ታስሮ እያለ በገንዳው ውስጥ ገብታ ስለሞተችው ስለዚህችው ልጅ አሟሟት ዙሪያ ግራ በመጋባት መስቀለኛ ጥያቄዎችን ሲጠይቁ በቦታው ነበርኩ፡፡ የወቅቱ የቆንስሉ ዘበኛ የነበሩት አቶ ገሬ ስለ ተፈጠረው ሁኔታ ማብራሪያ ሲሰጡም ሟች ገና ከምሽቱ በግምት 4፡00 ሰአት አካባቢ  ወደ ካፍቴሪያው ግቢ እንደመጣችና የዓዕምሮ ህመምተኛ በመሆኗ ከመጮህ በቀር አድራሻና ስሟን ባለመናገሯ እጅና እግሯን በማሰር ወደ ጊዜያዊ መጠለያው እንዳስቀመጣት ተናግሯል፡፡ ከዚያም አቶ ገሬ ሲያስረዳ ከምሽቱ 2፡00 አካባቢ ግቢን በሙሉና ገንዳውን ጨምሮ ከሰወች ጋር በመሆን ቢያፈላልጋትም የውሃው ገንዳ ገበድ ያለ ብረት መዝጊያ ገርገብ ብሎ እንዳገኘው በመብራት ቢመለከትም ምንም ነገር እንዳላየ ገልጿል፡፡ አቶ ገሬ በማከል ሲናገር ብዙም ሳይቆይ ግን ልጅቷ ከገንዳው ገብታለች ብሎ በመጠራጠሩ ገንዳውን ለማስፈተሽ ለፖሊስ ጥሪ ማድረጉን ተናግሯል፡፡ ከዚያ ፖሊስ መጥቶ ገንዳው ሲፈተሽ የዚህች ሬሳ ተገኝቶ በፖሊሶች እንደወጣ በቦታው ተገኝቸ ለመረዳት ችያለሁ፡፡ በመጨረሻም የቆንስሉ ዘበኛ ለጥያቄ ወደ ጣቢያ መወሰዳቸውን ተመልክቻለሁ፡፡ እኔን ጨምሮ ዲፕሎማቶችና የኮሚኒቲ ሃላፊዎች ንጋት ላይ ወደ የቤታችን ተመልሰናል፡፡
   ይህ በእንዲህ እንዳለ በርካቶች ያበዱ የኮንትራት ሰራተኞች በቆንስሉ ግቢና በጊዜያዊው መጠለያ ከአርባ የማያንሱ በአሁኑ ሰአት እንደሚገኙ ከቆንስሉ ያገኘሁት መረጃ ያስረዳል፡፡ በቆስል ከዚህ በፊት ተጠልለው የነበሩ አንዳን እህቶች በቆንስሉ በተጠጋንበት ቆንስል መስሪያ ቤት ዘበኛ አቶ ገሬ በሴትነታቸው ሊያጠቋቸው እስከመደብደብ እንደደረሱ ለቆንስል መስሪያ ቤቱ መከሳቸውን በመረጃ ማቅረቤ አይዘነጋም ፡፡ ዛሬ በዚሁ ጉዳይ ያነጋገርኳቸው አምባሳደር መርዋን ከዚህ በፊት ስለተፈጸመው ጥፋት ጠይቄያቸው አስተዳደራዊ እርምጃ እንደተወሰደ ገልጸውልኛል፡፡  
   

Friday, July 27, 2012

የማለዳ ወግ . . ..የጅዳ ሙስሊማን ጉዳይ ! "ማን ይናገር የነበረ ፤ ማን ያርዳ የቀበረ !" እማኝ ፤ ምስክር እያለ ብዥታ ሊኖር አይገባም !

   ከዚህ በፊት ባስነበብኳችሁ የማለዳ ወግ "አክራሪ" ተብየውን አህመዲን ጀበልን ፤ ጓዶቹንና የመጅልስ ከፍተኛ ባለስልጣናትን ሳውቃቸው ! በሚል ያዘጋጀሁትን ዳሰሳ ወቅታዊ ወግ ላሰካካ ካለብኝ የግል የስራ ጫና በተጓዳኝ እዚህ እዚያ ስል ነው የሰነበትኩት፡፡ በተለይም ከአስራ አምስት አመታት በላይ በኖርኩበት አካባቢ የታዘብኩት ግልጽ እውነታ ቢኖር ሙስሊሙ ማህበረሰብ በመጅሊስ መሪዎች ላይ የሚያሰማው ሮሮ እያደር በመሪዎቹ ላይ እምነት ማጣቱና ጥላቻው ከፍ ማለቱን ነው፡፡ 

ከወራት በፊት ጥያቄውን ያቀረቡ አባቶች በከፊል
ከመንግስት ባለስልጣናት ጋር ሲመክሩ
እናም ከራሴ ጋር መክሬ ስለመጅልስ ሃላፊዎችና በጸሎተኛው ዙሪያ ሰለደረሱ እጅግ በጣም ብዙ በድሎች ለአመታት ከኦምራና ሃጃጅ ምዕምናን የተነገረኝንና የማውቀውን ፍንትው ያለ መረጃዎች ላለመጠቀም ወሰንኩ፡፡ አዲስ ከነዋሪው አዲ የሚነገረኝን መረጃ ብቻ ላቀርብ ከአሴ ጋር ቃል ገብቸ ተንቀሳቀስኩ፡፡ እናም ዘወር ዘወር ብየ ነዋሪው ልጠይቅ ወስኛልሁ መጅልሱን የሚያመሰግን አጋጥሞኝ ባያውቅም በጎ ጎን ካለው ለመጠየቅ አለያም የአዎልያን የመጅልሱ ይውረ መፈከር ከድ አድርገው ድምጻቸውን የሚያሰሙትን ድግሞ "ለምን መጅልሱ ይውረድ ትላላችሁ ?" ስል ልጠይቅ የተለያዩ ወገኖችን ለማነጋገር ያደረግኩት ሙከራ ጠንከር ያለ የእኔኑ የቀድሞ መረጃ የሚያጠናክር እንጅ የተለየ ሆኖ በማግኘቴ አልደነቀኝም ፡፡ በዚህ ሁኔታ ማስታዎሻየን ሞነጫጭሬ ሃሳቤን ላጋራችሁ ስንተፋተፍ ባሳለፍነው ሳምንት በጅዳ ስለተካሄደው የተቃውሞ ስብሰባ  ያልጠበቅኩት የተወለካከፈ መረጃ ሲነገር አጋጠመኝ፡፡ እናም መሪየን መልስ ወደ ሚያሻው አዞርኩት ! እማኝ ምስክር እያለ ብዥታ ሊኖር አይገባም ስል መረጃዎቸን ሰባስቤ ከዚህ ማስታወሻ ጋር ላደርስዎ ፈቀድኩ !  

   ለበርካታ ወራ በአዎሊያ እየተሰባሰቡ " መንግስት ከሃይማኖት ጣልቃ አይግባ!" የሚሉና " መጅልስ ይውረድ ! " በማለት ድምጻቸውን የሚያሰሙ ኢትዮጵያውያን ጥያቄ " አግባብነት ያለው ነው!" ሲሉ በሳውዲ አረቢያ ሪያድና በጅዳ ኢትዮጵያን ሙሊሞች ለአዎሊያው እንቅስቃሴ ድጋፋቸው በመግለጽ መንግስት ጉዳዩን መርምሮ መፍትሄ እንዲያፈላልግ አቤቱታ የማቅረባቸውን ይታወሳል ፡፡  በተለይም ከሳምንት በፊት በአዎሊያና በአንዋር መስጊድ የተቀሰቀሰውን ግጭት ተከትሎ ቁጥራቸው በርካታ ነዋሪዎች "መንግስት ጉዳዩን በአጽኖት ይመረምረውና መፍትሄ ሊሰጥበት ይገባል እንጂ መብታችን እናከበር ያሉ ዜጎችን በሃይል ለማንበርከክ መሞከር ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናል ! " የሚል አንድምታ ያለው ውይይት በማድረግ የአቋም መግለጫ መልዕክታችውን ሃምሌ 8 ቀን 2004 አ.ም ሲያቀርቡ የአይን እማኝ ነበርኩ፡፡ 


    ነዋሪዎች የመጀመሪያውን ጥያቄ ከወራት
    በፊት ለውጭ ጉዳይ ባለስልጣኑ ሲያስረክቡ
በእለቱ በተለይም በጅዳ በተደረገው ስብሰባባ  ስሜት ተጠራርተውና ለስራ ጉዳይ ወደ ኮሚኒቲው ካፊቴሪያ ጎራ ባሉበት አጋጣሚ እንደተሰባሰቡ የገለጹልኝ ነዋሪዎች ባደረጉት ስብሰባ የመንግስት ሃላፊዎች ስብሰባውን በመካፈል የነዋሪውን ስሜት በማድመጥ ለመንግስት ያስተላልፉ ዘንድ ቢጋበዙም ስብሰባው በህገወጥ መንገድ ያለ ፍቃድ የተካሄደ በመሆኑ ለመሳተፍ ፈቃደኛ አለመሆናቸው ነዋሪውን አስቆጥቶት ነበር፡፡ ምንም እንኳ የመንግስት ሃላፊዎች ስብሰብውን ባይካፈሉም ለሰአታት በተደረገ ሽምግልና የተሰብሳቢውን የአቋም መግለጫ ለቆንስል ሃላፊዎች እንዲረከቡ መደረጉን የኮሚኒቲው ም/ሊቀመንበር አቶ አህመድ አባ ጀበል ገልጸውልኝ ነበር ፡፡ በዚሁ ሽምግልናም ም/ሊቀ መንበሩን ጨምሮ የህዝብ ግንኙነትና የማህበራዊ አገልግሎት አስታራቂ ኮሚቴ ሃላፊዎች ባደረጉት ጥረት ፍጥጫውን በማርገብ መቻሉን በገለጹልም መሰረት ሙሉ ዘገባው እጥርና ምጥን ለማድረድ ተሞክሮ በጀርመን ራዲዮ ዜና መጽሄት ቀዳሚ ዜና በትንታኔ ሆኖ ቀረበ !


  በተቃውሞው በስብሰባ መጨረሻ ጉዳዩን ለመከታተል የሚችሉ ኮሚቴ ሲያዋቅሩ አሁንም በቦታም በመገኘት አስፈላጊ መረጃዎችን አግኝቻለሁ፡፡ ከዚያ ወዲህም ኮሚቴው እየሰራ ስላለው ስራና ስለ አጠቃላይ ግንዛቤን አገኝ ዘንድ የኮሚቴውን እንቅስቃሴው ለመረዳት ያደረግኩት ተደጋጋሚ ሙከራና ጥረት ግን አልተሳካም፡፡ ስለኮሚቴው በቅርበት ከሚያውቁት ለማጣራት ባደርግኩት ሙከራም የገመትኩት ተስፋ አስቆራጭ ዜና ደረሰኝ ፡፡ "ህገ-ወጥ" በተባለው ስብሰባ የተመረጡት የኮሚቴ አባላት በቆንስሉ እውቅና እንዳልተሰጣቸውና በዚህም ምክንያት ኮሚቴው "አለ" ከማለት "የለም" ማለቱ እንደሚቀል አሰተያየታቸውን የሰጡኝ ነዋሪዎች ፍርሃት ስጋቱን አጫውተውኛል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለም ከላይ በጠቀስኩት የመጅልስ መሪዎች ጉዳይ መረጃና አስተያየት ለማዳመጥ ሳነፈንፍና ከአንዳን ነዋሪዎች ጋር ባደረግኩይ ግልጽ ውይይት እንደ ተረዳሁትም በዚህ ስብሰባ መወያያ የተመከረባቸው አበይት ነጥቦች ሌላ መልክ ተሰጥቷቸው ሲነገሩ አጋጥሞኛል፡፡ ከዚህም አልፎ ስብሰባውን ባልተካፈሉ ነዋሪዎች መካከል የተዛቡ መረጃዎችን ሲተላለፉ በመስማቴ ደስታ አልተሰማኝም፡፡ አባቶች "ማን ይናገር የነበረ ፤ ማን ያርዳ የቀበረ !" 

 ከወራት በፊት የሃይማኖት አባቶች
                       መረጃዎችን ሲያሳዩ . . .
እንደሚሉት በቦታው ነበርኩና የእማኝነት መረጃየን ማቅረብ ተሰማኝ፡፡ በዚሁ ዙሪያ ያሰባሰብኳቸውን የተንቀሳቃሽ ምስልና የድምጽ ማስረጃዎች ግልጽ አደርግ ዘንድ ሃላፊነት ተሰማኝ ! የተፈጠረውን የመረጃ መፋለስ ብዥታ ለመቅረፍ ይቻላል ዘንድም የስብሰባውን ግልጽ ሂደት ያሳያሉ ያልኳቸውን አንኳር አንኳር ሃሳቦችን ለማቅረብ ዝግጅቴን ጨርሻለሁ፡፡ ያም ሆኖ የተንቀሳቃሽምስሎችን እርዝመት ከግምት ውስጥ በማስገባት ለማሳጠርና አላስፈላጊ ድግግሞች እንዳይፈጠሩ ሙከራ ማድረጌን ከተረዳችሁልኝ ደስ ይለኛል፡፡ በየረፈ መረጃውን በሶስት ክፍል ያዘጋጀሁት ሲሆን ከውይይቱ በኋላም በወቅቱ ከአንዳንድ ተሰብሳቢዎችና ከጅዳና አካባቢው ኮሚኒቲ ከፍተኛ ሃላፊዎች ጋር በስብሰባው ዙሪያ ያደረግኩትን ቃለ መጠይቅ በአራተኛ ክፍል የሚቀርበው ይሆናል፡፡ እማኝ ምስክር እያለ ብዥታ ሊኖር አይገባም የሚል እምነት አለኝና እነሆ የዝግጅቱን መግቢያ ይመልከቱ !

በዚህ ዙሪያ አስተያየትዎን የምቀበልዎ በደስታ ነው  !

ቸር ያሰማን !
ነቢዩ ሲራክ


Wednesday, July 25, 2012

የማለዳ ወግ . . . ድንቸ አልበሰለም ! "... ፖለቲካውን እያበሰሉ ይልኩልናል . . . እኛ "ትክክል ነው ውሽት ነው" እያልን እንፋጃለን !

ዶር እሌኒ
    ራት ልበላ ድንች ቀቀልኩ ! አልበስል ብሎ ቢያቸረኝ ፊቴን ወደ ኮምፒውተሬ አፍጥጨ በማለዳው ከወዳጀ ከወንድም ደስታው ወገኛውጋር የደመቀ ወግ ይዘናል፡፡ ኢን ቦክስ inbox በሚሉት የጓዳ በር ፡) ደሱ በወጋችን መሃል አንድ ጽሁፍ እንዳነብ ቆመኝ ፡፡ ለካስ እኔን እያጫወተም ያነብ ኖሯል ! ደስታው ወደ ጠቆመኝ  የዶር እሌኒ መጣጥፍ ሳመራ ፈጣኑ ወዳጀ ከዶር እሌኔ መጣጥፍ ግርጌ" ! ይሄ ነው እንግልዘኛ፤ የገባኝን ያህል ተረድቼዋለሁ ያለምንም አስተርጓሚ:: ጻፈችው ሴትዮዋ! ጭርጭር አድርገው ከቦታዋ "ሲያሽቀነጥሯት" እኔ ኢትዮጵያዊነቴን እንጂ ዘሬን አላውቅም ብላ አረፈች. . .የኛ ሀገር እንግልዘኛና ህልም እንደፈቺው ነው እንግዲህ:: አንብቧት እና የራሳችሁን ፍቺ ውሰዱ እናንተ ደግሞ::  "Ethiopia is ours, to claim, to build and to restore. Rather than engage in destructive ethnic bigotry, far better to embrace all of what we are and to build together a better future for our children. " እለኒ ዘውዴ ገብረመድህን:: " የሚል አስተያየቱን ለጥፎበት አገኘሁ ! የደሱን " ፓ" አድናቆቱን አውቃታለሁና እኔም እንደሱ እያዋራሁት ወደ ጠቆመኝ እያባበለ ውስጥ የሚሰረስረውን መረጃ በጥድፈት አነበብኩት ፡፡


. . .  በሚነሽጠው ግሩምና ድንቅ በሆነው የዶር እሌኒ መጣጥፍ ኢትዮጵያን ደግሜ ደጋግሜ አየኋት . . . እናቴን !. . . "የሰው ልጅ በቃላት መንፈስን እውን ይፈጥራል!" ምናምን እያልኩ በስነ ጽሁፍን ሃያልነት፤ የፈጣሪን የአፈጣጠር ረቂቅ ጥበብ እስከ መመርመር ያደረሰኝን ያህል አድናቆት ለአምላክ አቅርቤ ቃላት ላጣሁለት ማራኪ መጣጥፍ ከደሱ አስተያየት ለጥቄ ለጠፍኩ እንዲህ በማለት እኔም ለጠፍኩ . .  .

እውነት እውነት እልሃለሁ ደሱ በተዋበውና በረቀቀው የክቡር እህት ዶር እለኒ ዘውዴ ገብረ መድህን መጣጥፍ የዥጉርጉሩን የትውልድ ሃረግ መሰረት ክቡሩን ኢትዮጵያዊነትን ለማየት ችያለሁ ! ". . . Ethiopia is ours, to claim, to build and to restore. Rather than engage in destructive ethnic bigotry, far better to embrace all of what we are and to build together a better future for our children. . ." ዶር እሌኒ እውነት ብለዋል ! ኢትዮጽያ የኛ ናት በጋራና በመተሳሰብ የምንገነባት ! ሁሉም የመጣጥፉ ክፍሎች አስተማሪ ናቸው ! ለአድናቆት ቃላቶች ያጥሩኛል !"  
  ያ የሆነው ትናንት ነበር ! ምሽት ላይ ድንች ቀቅየ አልበስል ሲለኝ ኮምፒውተሬ ከፍቸ አሁንም በተደጋጋሚ የፌስ ቡክ ጓደኞቻችን ዶር እሌኒን  መጣጥፍ እየተደመሙ የሚለጥፉትን እያስተዋልኩ እናንተኑ ወደ ትናንቱ ትዝታየ መጎተቴ ያለ ነገር አይደለም፡፡ እንደ ትናንቱ ወደ ሰፋ ወግ ልወስዳችሁ ሳይሆን ምሽት ላይ ያጋጠመኝንና የፈጣሪን ስራ ለማድነቅ ነው ! ድንች እንደቀቀልኩ አትርሱ ! ከመከረኛዋ ፎቴ ላይ ኩርምትም ድህረ ገጾችን ስጎራጉርና ካፈጠጥኩበት ኮንፒውተር ያስነሳኝ ሆዴን የሸረሸረው ረሃብ ነበር !  ከሚገነፋፍል ከሚንተከተከው ብረት ድስት ውስጥ እየተቀቀለ ያለውን ድንች በማንኪያ ገልበጥ ገልበትካደረግኩ በኋላ ማንኪያውን ወርወር አድርጌ ሹካ ጨበጥኩ፡፡ ቀጠልኩና የድንቹን መብሰል አለመብሰል ለማረጋገጥ ወጋ ወጋ እያደረግኩት አቶ ድንች ግን አልበሰለም ! እየሞረሞረኝ ቢሆንም ረሃቡን ለመርሳት ወደ ፌስ ቡክ ዞር ስል "ልብ ካላየ አይን አያይም" የሚሉት በኔ ደርሶ ከ15 በላይ መልዕክትና ከ48 በላይ የወዳጅነት ጥያቄ ከኔው ገጽ ጫፍ ተደርድሮ ጠበቀኝ ! 
  ከቀናት በፊት እየሆነ ያወ ሲያሳስበኝ በሙስሊማን ላይ እየሆነ ያለው እጅግ በጣም ያሳዝናል ! ስል የጻፍኩት ማስታወሻ ዋንኛ ምክንያቱ በሙስሊም ወገኖቸ ላይ እየሆነ ያለውን ዙሬ አዟዙሬ ሳየው አልዋጥልህ ስላለኝ ነበር፡፡ ይህ ሆነና እውነቱ የልቤን አውጥቸ በማጋራቴ ብዙዎች ደስታቸውን በአካልና በስልክ እየደወሉ የገለጹልኝን ያህል በፌስ ቡክ ገጼ ላይ ለወዳጅነት የሚጠይቁኝ ቁጥር ተበራክተዋል፡፡ እኔም ቢሆን የማምንበትን እምነት ለማራድ ነፍሴ ከፈቀደ ከራርሟልና ማንም ይሁን ማን ለወዳጅነት ከፈቀደኝ በሬን ወለል አድር ከከፈትኩት ቆይቻለሁ ፡፡ ያም ሆኖ በአንድ ቀን ውስጥ እንዲህ በጥቂት ሰአታት ልዩነት ጉድኝነት ጥያቄውና መልዕክቱ እንዲህ ሆኖ አይቸው አላውቅምና "ምን አዲስ ነገር ተፈጠረ " ስል ራሴን መልሸ መላልሸ መጠየቄ ባይቀርም በጻፍኩትና በምጽፈው ዙሪያ ራሴን መየቁ አላስፈለገኝም፡፡ አስረግጨ የማውቀውንና ነፍሴ የፈቀደውን ስለማደርግ ራሴን ዞሮ ማጠየቁን አልደፈርኩትም ፡፡ ብቻ ይህ አጋጣሚ በጉዳዩ ዙሪያ እየሆነ ያለውን እንድመረምር ጋበዘኝ. . . የሙስሊማን ሰላማዊ መብት ጥያቄ ሲነሳና ሃሳቤን ስገልጽ ያገኘሁት ህብረት የሚታይበት ምላሽ   ወደ አንድ መጣጥፍ እንዳመራ አስገደደኝ ! "ድር ቢያድር "ብየ ጀመርኩትና እንደገና ረዝኩት . . . ደጋግሜ የተለያዩ ርዕሶችን አውጥቸ አወረድኩና የመጨረሻዋን ተስማሚ ርዕስ በብዕሬ ቀለም በነጩ ወረቀት ላይ ከተብኩ"የዜጎችን ህብረት የሚሹት የሙስሊማኑና የኮንትራት ሰራተኞች ህገ መንግስታዊ የመብት ጥያቄዎች ሲዳሰሱ !" በሚል ርዕስ ዙሪያ የኮንትራት ሰራተኞችን አበሳና የመብት ይከበርልኝ ጥያቄ ከሙስሊማኑ ሰላማዊ ህገ መንግስታዊ የመብት ጥያቄ ዚሩያ በቀጣይ ቀናት ለመዳሰስና ለመንሸርሸር ወሰንኩና ይህንንም በዚህ ዘግቸ ወደ ወቅቱ ምልከታየን ቀጠልኩ፡፡ . . . . . .
 ይሄ የኔ ድንች በቀላሉ እንደማይበስል ስለተረዳሁ "ትንሽ ሳት ይምታው ይብሰል!" በማለት ተውኩት፡፡ ድንቸ ሙክክ ብሎ እስኪበስል መልዕክቶችን ማንበብ ጀመርኩ፡፡ ባንድ ወቅት የጅዳ ቆንስል ከፍተኛ ሃላፊ ከነበሩ ወዳጀ ጀምሮ የማላውቃቸው በርካታ ወገኖቸን መልዕክት በደስታ ነበር የቃኘሁት፡፡ የቆንስሉ ሃላፊ ያልኳችሁ ሰው መልዕክት ሰላምታ ብቻ እንጂ እንደቀሩት ወገኖቸ መልዕክት ወደ ምስጋና ሆነ ወደ ሌላ ጉዳይ አልዘለቁም፡፡ የቀሩት የዛሬ ምሽት መልዕክቶች ግን ተመሳሳይ የአድናቆትና የምስጋና ብቻ ነበሩ ማለት ይቻላል፡፡ የሚገርመው ነገር ቢኖር ከተደረደሩት ሁሉ መልዕክቶች አንድም የሚያስከፋ መልዕክት አለመኖሩ ነው፡፡ ፍጹም ስሜትን የሚነኩ ምስጋናዎች ነበሩ ! ለተጻፈልኝ አስተያየትና ምስጋና ሁሉ ተገቢውን ምላሽ ሰጥቸ ብዙሃን ባደነቁት ባወደሱት ወገኖቸ ቀዳሚ ነገር ዙሪያ ለጀመርኩትን መጣጥፍ ግብአት የነዋሪውን አስተያየት ለመሰብሰብ መንቀሳቀስ የጀመርኩ ከመሸ ነበር፡፡ "አክራሪ" ተብየውን አህመዲን ጀበልን ጓዶቹንና የመጅልስ ከፍተኛ ባለስልጣናትን ሳውቃቸው ! በሚል ለጀመርኩት መጣጥፍ በከተማው መናኘቱን የተረዳሁት መረጃ ለመሰባሰብ በከተማው ሽሻ ቤቶችና በኮሚኒቲው አዳራሽ ጎራ ባልኩባቸው አጋጣሚዎች ያገኘኋቸው ወዳጆቸ ሞቅ አድርገው ከመጨበጥ ባለፈ እያቀፉ ሲስሙኝ አልነበረም፡፡ በቀጥታ የሳውዲ ኢትዮጵያውያን ብሶትና ሃሳብ ይገልጻል ባሉት" የመጅልስ ይውረድ!" ጥያቄ ዙርያ ብዙ አወጋን፡፡ በመጅሊስ ሃላፊዎች አይዎክሉንም የሚለውን ለማጠናከር በነዋሪው የሚነገሩና የሚሰነዘሩ አስተያየቶች እኔ ከምለው ጠንከር ያሎ ሆነው አገኘኋቸው፡፡  እንዲህ እንዲያ ስል አምሻሽቸ ወደ ቤቴ ተመለስኩ. . .  
 አሁን ለአንድ ሰአት ያህል የተጣደው ድንቸ እንደበሰለ እርግጠኛ ነኝ ፡፡ ፈንጠር ብየ ከፎቴው ተነሳሁና ወደ ጓዳ አመራሁ ! ሹካውን ይዥ የሚንፈቀፈቀውን የፈላ ውሃ አልፌ ድንቹን ወጋ ወጋ ሳደርግ ሞከክ ብሎ በስሏል፡፡ የድስቱን ሁለት ጀሮዎች በጨርቅ አፈፍ አደርጌ ወደ ቧንቧው በመውሰድ የፈላውን ሙቅ ውሃ በማፍሰስ የቧንቧ ውሃ ቸለስኩበት ! እንፋሎቱ ተጉለል ሲል ደጋግሜ በቸለስኩት ውሃ ድንቸን አባርደኩ፡፡ እርቦኝ ልበላ ስንገበገብ ከተቀቀለው ድንች መካከል አስገራሚ የልብ ቅርጽ ያለት አንዲት ድንች አይኔን ሳበችው ፡) እንደ መሳቅ እንደ መገረም እያልኩ ካፈጠጥኩበት ኮንፒውተር ዳር ድንቸን አስቀምጨ የፈጣሪ ስራ ለማድነቅ ፎቶ ማንሳት ያዝኩ ! በአጋጣሚዎች ሁሉ ተደመምኩ ጠዋት በዶር እሌኒ አእምሮን የመጨምደድና የመግዛት ሃይል ባላቸው ህይዎትን የሚሰጡ ማራኪ ቃላቶች ፤ ምሺት ላይ በአስገራሚዋ የልብ ቅርጽ ያላት የኔ ድንች የፈጣሪን ድንቅ ስራና ተአምር  በማድነቅና በሃያልነቱ ቸርነት ይማለደን ዘንድ ተማጽኘ ጽሁፌን ልቋጭ ስንደፋደፍ ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት ደሱ ወገኛው አንድ የለጠፋት ቁም ነገር ሳበችኝ፡፡ እያደገ ያለው እስላም አክራሪነት በኢትዮጵያ የሚል መንፈስ የዋሽንግተን ፖስት ጋዜጣ ግጭቱ ተንተርሶ በእንግሊዝኛው የሰጣት አስተያየት "Here you go!

They cook their politics and they send to us. Then we fight saying "Yes it is True", "No it is false". . . Then they film our fight and enjoy switching on their remote control!" የደሱን አስተያየት በድፍረት ስተርጉማት እንዲህ ትላለች  " ይህውላችሁ ! ተመልከቱ ! ፖለቲካውን እያበሰሉ ይልኩልናል . . . እኛ "ትክክል ነው ውሽት ነው" እያልን እንፋጃለን . . . ከዚያም ፍጅታችን ይቀርጹና ተደላድለው በሚዘውሩት የቴሌቪዥን ምስል መቀያየሪያ remote control እየቀያየሩ በደስታ ፍጅታችን ይፈረጁታል !" ያላት ቀልቤ ሳበችው ! አዎ ዜናውን አነበብኩት እንደተባለው የአሜሪካ የጸረ ሽብር አግር በሆነቸው በሃገራችን መንስግትና በሙስሊማን መካከል የተቀሰቀሰው ግጭት ምንጩ እኔን እስከገባኝ ድረስ የኢትዮጵያን ህገ መንግስጽ አንቀጽ ሶስት ላይ “ መንግስት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም ፤ ሃይማኖትም በመንግስት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም” በሚል የተደነገገው ይከበር የሚል ህገ መንግስታዊ የመብት ጥያቄ እንጂ  በመንግስት መገናኛ ብዙሃንና ዛሬም በዋሽንግተን ፖስት ጋዜጣ ሊገለጽ

ሚስጥር ዘክዛኪው ዊክሊክና አሳንጅ
እንደተፈለገው ግጭቱ በመንግስት ወታደሮችና በሃገሪቱ እያደጉ በመጡት ሙስሊም አክራሪነት መካከል አይደለም፡፡ ትክክለኛ መረጃ አይደለም፡፡ ይህ ዘገባ የአሜሪካው አምባሳደር ዶር ያማማቶ ወደ አሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ያስተላለፉትን አፈትልኮ የወጣ ሚስጥራዊን የዊክሊክ መረጃ አስታወሰኝ፡፡ እንደ መረጃው ከሆነ የቀድሞው በኢትዮጵያ የአሜሪካው አምባሳደር ዶር ያማማቶ በግርድፉ ያሉት እስላም አክራሪነት "በውሃቢይዝም" ጀርባ በኢትዮጵያ ውስጥ የመስፋፋት አዝማሚያ ማሳየቱን ነበር፡፡ ችግሮች አልተስተዋሉም ብየ አልከራከርም ! ያም ሆኖ አሁን በተነሳው የሙስሊማን የመብት ጥያቄ ዙሪያ የአክራሪነት መንፈስና ጥያቄ ሃገሬን ይንጣታል ብየ አልሰጋም ፡፡ ያ መንፈስ አለ ሊያስብል የሚያስችል እውነታ የለም ባይ ነኝ ! ብቻ ሁኔታውን ረጋ ብለንና ከስሜት ወጥተን በውል ማጤን ይገባል ስል ለዚህ ሁሉ ተንኮል ወደ ማይተኙት እጀን በመጠቆም ነው . . . የደሱን አስተያየት ልድገም  "  ፖለቲካውን እያበሰሉ ይልኩልናል . . . እኛ "ትክክል ነው ውሽት ነው" እያልን እንፋጃለን . . . ከዚያም ፍጅታችን ይቀርጹና ተደላድለው በሚዘውሩት የቴሌቪዥን ምስል መቀያየሪያ remote control እየቀያየሩ በደስታ ፍጅታችን ይፈረጁታል !" ለሁሉም እውነቱን ገላጭ ለሆነው ፈጣሪ እውነቱን እንዲያሳየን በመማጸንና ለድንቅ ስራው በማመስገን የማለዳ ወጌን እቋጭ ዘንድ አሁንም የሱ ፈቃድ ሆነ !
ቸር ያሰማን !
ነቢዩ ሲራክ


Monday, July 23, 2012

በሙስሊማን ላይ እየሆነ ያለው እጅግ በጣም ያሳዝናል !

       በእኒህ ወጣት ሙስሊም ወንድሞቻችን ላይ እየሆነ ያለው እጅግ በጣም ያሳዝናል ! የሙስሊም ወንድሞቻችን ላይ በግፍ መታሰርና አስከፊ አያያዛቸው ያበሳጫቸው በአረብ ሃገር የሚኖሩ ክርስትያንና ሙስሊም ወንድሞች ስልክ በመደወል የተሰማቸውን ሃዘን በተደጋጋሚ ገልጸውልኛል፡፡ ብዙዎች ጉልቻ ቢቀያየርም ወጡ አልጣፍጥ ብሏል እያሉ ይመስላል . . . . ጃንሆይ አውግዘን ደርግን ባመጣን ማግስት በርቀት የሰማነው ሁሉ የአፈና ፤ የግድያና የሰቆቃ ዘመንን በራሳችን ላይ ተጫነብን ! ከ17 አመት መሪር ትግል በኋላ ደርግን አሽቀንጥረን ጣልን . . . ይህው ላለፉት ሃያ አንድ አመት ሀገሪቱ በአንድ አውራ ፓርቲና በአንድ መሪ ስትመራ ፓርቲው ታገልኩለት ያለ ዲሞክራሲና ነጻነት ማግኘት አልቻልንም ! ሌላው ቀርቶ የፕሬስ ነጻነት አንድ አፍታ ታይቶ ጠፋ እንጅ አልቀጠለም ! ያለመታደል ሆኖ ነው መሰል ደርግ በተቃዋሚው ላይ አደረገ ስንል ስናዎግዘው የነበረው እስራት ፤ የአፈና ፤ አሰቃቂ ድብደባ ፤ የግድያና የሰቆቃ ጊዜ አላከተመም !
 ይህን ሁሉ ያስታወሰኝ በኮሚቴዎ ደረሰ የተባለው ድብደባ እስራትና የምሽቱ የኢቲቪን ዜና ነበር ፡፡ ዜናውን እንደለመድኩት  እያመመኝ ሰማሁት፡፡ ብቻ ፈጣሪ ይህችን ሐገር ጥሎ አይጥላትም እንጅ በመንግስት መገናኛ ብዙሃን በሚቀርቡ ውልን ያሳቱ መረጃዎች ምን ያህል አብዛኛውን ንጹህ ህዝብ በጥፋት ማዕበል ሊያሰልፍ እንደሚችል ሳስበው አዘንኩ !  በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሙስሊም ምዕመናን መረጥናቸው ያሏቸው ኮሚቴወች እየታደኑ ሲያዙ የመንግስት መገናኛ ብዙሃን በተለይም የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የሚያቀርባቸው ኮሚቴውን "ጽንፈኛና አክራሪ" እያሉ የሚያወግዙ ሰላማዊ ሰልፎች በያዝነው ሳምንት ለእርምጃ እንዲመቹ ተደርገው እየተበራከቱ ሄደዋል፡፡ ማለዳ ላይ በስልክ ወደ ሃገር ቤት ስደውል ያገኘሁት ወዳጀ የጎንደርና የጎጃም ሙስሊማንም ሰላማዊ ሰልፍ ውጡ ተብለው በየቀበሌው በግዴታ መቀቀሳቸውን ሲያጫውተኝ ስላማዊ ሰልፉን ለማይሳተፉ ከስኳር እደላው እንደሚገለሉ እንደተነገራቸው አጫውቶኛል፡፡ ሃይል እስካለ ድረስ ተፈላጊዎችን ማሰርና እየሆነ ያለውን ማድረግ እየተቻለ ሰላማዊውን ነዋሪ ቂም ሊያቃባ የሚችል ፕሮፓጋንዳ ለምን እንዳስፈለገ አልገባኝም፡፡

በሰለጠነው በዚህ በኛ ዘመን ከሃያ አንድ አመት  በፊት የደርግን ዘመን መልሸ መላልሸ ለማስታዎስ ተገደድኩ . . .ደርግ ጭንቅ ሲለው ህዝብን ማስተባበርና ማዝመት ሲያሻው ብቻ ሳይሆን ጥላቻን ሲዘራብን የዛሬውን መንግስት ባለስልጣናት የአጥፍቶ ጠፊ ደቀ መዛሙርት ያደርጋቸው ነበር፡፡  በደርግ  "የሻቢያና ወያኔን ሀገር ገንጣዮች እናዎግዛለን " በሚል በመጨረሻዋ ሰአት ሳይቀር ይተወን የነበረውን ያላታደለውን የኢቲቪ የያኔ ዘገባ ከፊት ከፊቴ ድቅን አለ . . .ዛሬም አብዛኛው ድጋፍ እያገኑ የመጡትን  "ጽንፈኛና አክራሪ" ኮሚቴዎች እያስባለ የሚኬደውን መንገድ ሳስበው ከቀናት በፊት በአንዋር መስጊድ ተሰባስበው በሰላማዊ መንገድ "መሪዎቻችን ይፍቱ !" የሚል ድምጽን የሚያሰሙ ወንድሞቻችንን ውሎ ከሚያሳዩት ተንቀሳቃሽ ፊልሞች መካከል 12 ደቂቃ በሚሆነው በአንዱ ፊልም ያየሁት የወገን ድምጽና የምሬት እንባ  መንፈሴን አሰቃየው ! እውንም ይህ ሰላማዊ የመብት ጥያቄ "ጽንፈኛና አክራሪ"ነት ነው ተብሎ ፕሮፓጋንዳ ሊሰራበት ይገባ ነበርን ? ስል ራሴን ብጠይቅም መልስ አላገኘሁም ! ለነገሩ በአንባገነኖች መንደር ይህ መሰል ፕሮፓጋንዳ የተለመደ መሆኑን ላፍታ አዘከርኩት ! አዎ በአረብ ሀገሩ አብዮትም ይሰራ የነበረው ፕሮፓጋንዳ ይህን መሰል የማይጨበጥ ነበር ፡፡ የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ፕሮፓጋንዳ ሌላ ፤ እውነቱና  እየሆነ ያለው ሌላ ለመሆኑ በጋዳፊዋ ትሪፖሊ ፤ በሙባረክ ካይሮ ፤  በአሊ አብደላ ሳላህ ሰንአና በበሻር ደማስቆ ያየነውና እያየነው ያለው በተመሳሳይ ሁኔታ የተቀነባበረው ትዕይንት ተመልክተናል ! ትናንት በጃንሆይ የጃንሆይን ካባ ፤ በድርግ የደርግን ካባ ደርቦ እንዲያ ሲያቦኩ የነበሩት የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ዘርፎች ዛሬ የኢሃዴግን ካባ ደርቦ ተመሳሳይ ስራቸውን ሲገፉት ያለንበትን የሰለጠነ አለም ከግምት ያስገቡት ቢሆን ምንኛ ደግ ነበር ! የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ያሻቸውን ሲደሰኩሩ እድሜ ለሰላጠነው ቴክኖሎጅ  በቅርቡ የአንዋርንና የአዎልያን ግጭት ተከትሎ ዩትዩብን በመሳሰሉ በተለያዩ ድህረ ገጾች የተለቀቁ ፎቶዎችና ተንቀሳቃሽ ፊልሞች እያወጡት ያለው መረጃ  የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ራቁት ያስቀረ ሃቅ ለመሆኑ ፊስ ቡክን ከፈት አድርጎ አንዳፍታ መመልከት ብቻ ይበቃል ! ይህን ሁሉ አዙሮ ላየው በአብዛኛው ኢትዮጵያዊ በሃገሩ በነጻነት እየኖረ ነው ለማለት የሚያስደፍር ነገር ይኖር ይሆን ! ?