Wednesday, May 9, 2012

የኮንትራት ስለሚመጡ ዜጎች የኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ አባል ድርጅትን አቋም የሚገልጸው ሰነድ. . . !


የደ.ኢ.ህዴ.ን አቋም መግለጫ ሰንድ 4ኛ ገጽ
  አመሻሹ ላይ የደቡብ ኢትዮጵያ ህዝቦች የጅዳ መሰረታዊ ድርጅት የጅዳ መሰረታዊ ድርጅት (ደ.ኢ.ህዴ.ን) ለእናት ማህበሩ ለኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ "በቪዛ የሚመጡ ወገኖችን ይመለከታል" በሚል ፍሬ ሃሳብ ስር ያሰፈው አራት ገጽ ዝርዝር መግለጫና የውሳኔ ሃሳብ የተዘረዘሩ ቁም ነገሮችን ያካተተው የደብዳቤ ኮፒ በኋላው በር ደርሶኝ በጽሞና ደግሜ ደጋግሜ ተመልክቸዋለሁ፡፡  ከሁሉም በላይ በውሳኔ ሀሳቡ ላይ የቀረበው የአቋም መግለጫ መላ ነዋሪውን በአንድ ማዕቀፍ የሚያሰባስበውን የጅዳ ኮሚኒቲና የጅዳ ቆንስል መስሪያ ቤት በመጠላያ የሚገኙትን ለግፉአን ወገኖችን ለመደገፍ ለመደገፍ የጀመሩትን እንቅስቃሴ "ይፋዊ ባልሆነ መንገድ ሰምተነዋል" ይልና ኮሚኒቲው ይህን መሰል ሃላፊነት መወጣት አይችልም በማለት ያትታል፡፡ ለዚህም የኮሚኒቲውን ብቁ አለመሆን በሚያኮስሰው አምስት የማይስማሙ ምክንያቶች አምስተኛ ተራ ላይ አነሰም በዛ በአባላት ይሁንታ የተመረጡ የአመራር አባላት ላይ ያነጣጠረ ወቀሳውን ይሰነዝራል፡፡ እንዲህ በማለት እጠቅሳለሁ"በኮሚቲው አመራር ውስጥ በሃገራችን የገጽታ ግንባታ ስራ ውስጥ ፖለቲካዊ ዝግጂት የሚጎላቸው አባላት አሉ፡፡" ይላል፡፡ የደቡብ ህዝቦች ንቅናቄ ኮሚኒቲው ከዚህ መሰል እንቅስቃሴ እንዳይሳተፍ ለኢ.ህ.አ.ዴ.ግ የጅዳ ጽህፈት ቤት በላከው የውሳኔ ሃሳብ ደብዳቤ ቆንስል መስሪያ ቤቱ በበላይነት እንዲመራው በመምከር ሲያስረዳም ይህን መሰሉን ጉዳይ ለመፍታት የተቋቋመው ኮሚቴና የሴቶች ማህበርን በማጠናከር ስራው መሰራት እንዳለበት አቋሙን በአጽንኦት ይጠይቃል፡፡



ልትደፈር ስትል አመልጥ ብላ ከፎቅ ዘላ ሁለት እግሯን የተሰበረችው እህት
  በአስገራሚው ሰነድ የተጠቀሰው ሁሉ አነጋጋሪ ቢሆንም በገጽ ሁለት ላይ የተፈናቃዮች ቁጥር ከፍ እያለ እንደሚመጣ በማመላከት ችግሩ እየከፋ ከቁጥጥር ውጭ እንዳይዎጣ ስጋት መኖሩን በማመላከት መፍትሄ ሃሳቡን ያመላከተበት አቅጣጫ አሳዛኝ ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡ ሁሉንም ዜጎች በዘር ሳይለይ ያቀፈውና በአረንጓዴ ቢጫ ቀይ ባንዴራ ስር የተደራጀው ኮሚኒቲን አጣጥሎ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በመንግስት ከፍተኛ ጉትግታ የተቋቋመውን የሴቶች ማህበርና የመፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴው ሃላፊነቱ እንዲሰጣቸው መጠየቅ ለተቸገሩት ማዘንና ለዜጎች ደህንነት ከመቆርቆር የመነጨ አለመሆኑን ለመስገንዘብ ብዙ መሄድ ያለብኝ አይመስለኝም፡፡ የሴቶች ማህበር ለስንተኛ ጊዜ ተመስርቶ ተደራጀ ? ከዚህ በፊት በተለያዩ ዝግጅቶች የተሰባሰበው ገንዘብ የት ገባ ? የአሁኑ ማህበርስ አባላት ስንት ናቸው ? እነማን ?  ብለን ከመጠየቅ አልፈን የአሁኑ ማህበር አሁን የተሰጠውን ሃላፊነት የመወጣት አቅም አለው ብለን ከጠየቅን ከኮሚኒቲው የተሻለ ሆኖ እንደማናገኘው በእርግጠኝነት መናገር ይችላል፡፡ ሌላው ስራውን እንዲሰራ በውሳኔ ሃሳቡ የተጠቀሰው የመፍትሄ አፈላለጊ ኮሚቴ ሆኖ ስናገኘው ሌላውን እንቆቅልሽ እናገኘዋለን፡፡ የመፍትሄ አፈላለጊ ኮሚቴው ላለፉት ሰባት አመታት መኖሩ እንጂ እየሰራው ስላለው ስራ ፤ ከነዋሪው በየቀኑ የሚሰበስበው ከመቶ ሽዎች ያለፈ ገንዘብ አንድም ቀን ለመረጠው ምልአተ ጉባኤ ሪፖርት አቅርቦ የማያውቅ በጣት በሚቆጠሩ ወገኖች የሚመራ ግልጽነት የማይታይበት አካል ለመሆኑ ብዙ ማለት ይቻላል፡፡ ኮሚቴው እየሰራ እያለው ግራ ያጋባቸውና ጉዳዩ ያገባናል ያሉ ወገኖች ፊርማ በማሰባሰብ እየተሰራ ስላለው ስራ ይገለጽልን ! በአዲስ ይደራጅ አለያም መዳረሻውን እንወቀው በማለት ያቀረቡት አቤቱታ በኮሚኒቲው በኩል ለቆንስል መስሪያ ቤቱ የቀረበ ቢሆንም ላለፉት ወራት ለዚህ የተሰጠ መልስ የለም፡፡ አሁንም በዚህ እንዘርዝር ከተባለ ብዙ ማለት ይቻላል፡፡ ለጊዜው ይቅር ! አዎ ከላይ በድርጅቱ የቀረበው ውሳኔ ሃሳብን አስተዛዛቢ የሚያደርገው ይህ ግልጽነት ያልተሞላበት ድብቅ እውነት በተባሉት ማህበራት ጫንቃ ተቆልሎ ፍንትው ብሎ ሰብ አዊነት ብቻ የሚተይቀውን ስራ ኮሚኒቲው የመሸከም አቅም የለውም ብሎ መናገር ከነባሪው እውነታ መሸሸት ነው ብሎ መደምደም አስተዛዛቢ ብቻ ሊሆን አይችልም፡፡ከዚህ ተነስተን እውነታውን ስንገመግም የኮንትራት ስለሚመጡ ዜጎችና በኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ አባል ድርጅትን የሚያስረዳው ሰነድ መፍትሄ አመላካች ሊሆን ገና ቡዙ ብዙ ይቀረዋል !


          ለወራት የጎስቋሎች የቆንስሉ መጠለያ  ውሎ . . .

  ዜጎች ስራ ብለው መጥተው ያልጠበቁት የመከራ ቀንበር ተጭኗቸው ባለበት የታሪክ አጋጣሚ አሁን በኢ.ሕ.ዴ.ግ አባል ድርጅት፤ በጥላው ስር ባሉ ድርጅቶና በኮሚኒቲው መካከል የሚታየው ፍጥጫ  መቆም ይኖርበታል፡፡"አለባብሰው ቢያርሱ ባረም ይመለሱ" ይላሉ አባቶች ፡፡  አለባብሰን ማረሱ የትም አያደርሰንም፡፡ ለማድረግ የተፈለገው ተፈናቃይ ወገኖችን መደገፍ ከሆነ መፍትሄው አንድና አንድ ብቻ ነው ፡፡ ተፈናቃይ ወገኖችን በህብረት ተባብረን ከመደገፍና ከመታደግ አልፈን በተንኮም ስንነቋቆር ፤ በፖለቲካ ስንጠላለፍ እንደባጀነው በቀጣይነት በዚህ እኩይ ምግባር መዛቀጥ የለብንም፡፡ አባቶች ያቆዩን የመተዛዘንና የመደጋገፍ ባህል ባልረባባ ተሰባሪ ፖለቲካ ከበከልነው  የድረሱልኝ ጥሪ የሚያስተጋቡ ወገኖችን ጥሪ ከመስማትና በህብረት ልንታደጋት ከምንችለው የብዙሃን ወገኖች ህይዎት ማዳን በጎ ምግባር ያራርቀናል የወገኖቻችን እንባ መጥረጉና ማዳኑ ታላቅ ተስፋ አንድ አምላክ ቢሆንም ከሱ በታች በቸርነቱ የተጨነቀችን ነፍስ መድረስ የሁላችንም ግዴታ ነውና ! ይህ ቅን ተግባር የሁሉም ሃይማኖት ተከታዮች ፤ የሁሉም ቋንቋ ተናጋሪዎች ፤ የሁሉም ዜጎች ድርሻ ነው። የዜጎች መብትን ሳናስጠብቅ ዘላቂ እድገት አና ልማት ልናመጣ አንችልም። የሀገር ድንበር ተደፈረ ፤ ወገን በረሃብ በቸነፈርና በጎርፍ አለቀ፤ ዛሬም የአባይን ድልድይ ልንሰራ ነው ፤  ብለን ቅኔ ቋጥረን ፤ አነቃቂ ጥኡመ ዜማን ደርድረን፤ በፉከራና ቀረርቶ በአንድነት የተነሳነውን ያህል ከጫፍ እስከጫፍ መንቀሳቀሱ በፖለቲከኞቻችን "የሃገርን ገጽታ ያጎድፋል!" እንኳ ቢባል በዜጎች ላይ እየደረሰ ላለው እየከፋ ለመጣው ነግ በኔ ነውና መላ ልንዘይድለትና በአንድነት ልንሰራ ይገባል መልዕክቴ ነው!  


              

Monday, May 7, 2012

አይን ያለው ይመልከት ፤ ጀሮ ያለው ይስማ ፤ እዝነ-ልቦና ያለው ራሱን ይጠይቅ !

 ከስራ የሚፈናቀሉት የኮንትራት ሰራተኞች ቁጥር ከቀን ወደ ቀን እየጨምረ መጥቷል፡፡ በሚደርስባቸው የስራ ጫና ፤ በስራ ሰአት ብዛት ፤ የጤና መታዎክን ተከትሎ ህክምና ስለማያገኙ፤ ለሃገሩ ባዳ በመሆንና ከአካባቢውና ከስራው ጋር ራሳቸውን ባለማዋሃድ የሚያብዱ ፤ በአስገድዶ መድፈር ጉዳት የደረሰባቸውና ያረገዙ ጭምር በሪያድ ኢንባሲ የኮሚኒቲ መጠለያና በጅዳ ቆንስል ግቢ ያለ በቂ መጠለያ ሲንገላቱ ተመልክተናል ፤ እየተመለከትንም ነው ! የሪያድ ተጠላዮች ያበዱትን ከአራት በላይ እህቶች ጨምሮ ከ30 በላይ እህቶች ያሉበት ሁኔታ ከጅዳው የከፋና ብዙ አነጋጋሪ እየሆነ መምጣቱን በተደጋጋሞ በቦታው ተገኝቸ ተመልክቻለሁ ፡፡ የግፉአን እህቶችን ችግር ከጓሯቸው ሄደው በመመልከት መፍትሄ በማፈላለግ እንደመፍታት የተያዘው ምርመራ ደስ አያሰኝም፡፡ ምርመራው እህቶች የፍጥኝ ታስረው ሲጮሁ የሚያሳየውን ይህ አሳዛኝ ተንቀሳቃሽ ምስል (ቪዲዮ) ያነሱት እነማን ናቸው ? ከሚል ጥያቄ ተጀምሮ ጥያቄና መልሱ እስከ ማስፈራራት የዘለቀ እንደሆነ ተረድቻለሁ፡፡ ቪዲዮ አነሱ የተባሉት ሁለት ወጣቶች ሪያድ በሚገኘው ኢንባሲ ቀርበው ተንቀሳቃሽ ካሜራቸውን መቀማታቸን ሰምቻለሁ፡፡ ይገርማል ! የመንግስት ሃላፊዎቻችን መብቱን ሳያስከብሩለትና ሳይጠብቁት ቀርቶ በወገን ላይ የሚደርሰውን ግፍ ሰሚ ይገኝ እንደሁ ያነሱት ወንድሞች  ለማለት እንደተፈለገው "የሃገርን ገጽታ ለማበላሸት" የሚንቀሳቀሱ አይመስሉኝም፡፡ ይልቁንም ለተቸገሩት ውሃና ምግብ ያቀብሉ እንደነበር በቦታው ያገኘኋቸው ገልጸውልኛል፡፡ ያም ሆኖ መብታቸውን ማስከበር ቀርቶ ውሃ ያላቀበሉት ያልሆነ ስም እየለጠፉ ቅን አሳቢዎችን እስከማወገዝ የተንደረደሩበት እርምጃ ይስተዋላል ፡፡ ይህም ደስ አይልም ! እርምጃው " ሌባን ያዙ !" ያለን ጠቋሚ እያሳደዱ ሌባውን ከመልቀቅ ያልተናነሰ ነው ቢባል ማጋነን ይሆን ?

 በጅዳ  ቆንስልም እስከ ትናንትናው እለት ስድስት አዕምሯቸውን የሳቱ (ያበዱ) እህቶችን ጨምሮ ከላይ በጠቀስኳቸው በተለያዩ ችግሩች የተዳረጉ ከ38 በላይ የኮንትራት ሰራተኞች በቆንስሉ ግቢ ታዛና በጠባቧ መጠለያ ተጠልለው ሰንብተዋል፡፡ "ቆንስል መስሪያ ቤቱና ኮሚኒቲው በጥምረት በመስራት ለዘላቂው ችግር መፍትሄ ማፈላለግ ቢሳናቸውም እንዴት መጠለያ እንኳ በአግባቡ አያዘጋጁም ? " በሚል የሰላ ሂስ በነዋሪው እየተሰነዘረ ይገኛል ፡፡ በአንጻሩ ኮሚኒቲና ቆንስል መስሪያ ቤቱ ችግሩን ለመቅረፍ  አማራጭ ፕሮጀክቶችን መንደፋቸውን በጓዳ በር በሚያደርጓቸው ስብሰባዎች በጓዳ በር ይፋ እየሆነ መስማታችን አልቀረም፡፡ ትናንት ምሽት ደግሞ በቆንስል መስሪያ ቤቱ ተጠልለው የነበሩት የኮንትራት ሰራተኞች ወደ ሌላ መጠለያ መላካቸው አነጋጋሪ እርምጃ ሆኗል፡፡ ቆንስሉ ወደ አዘጋጀው አዲሱ መጠለያ ሂዱ ሲባሉ "አሻፈረኝ" ያሉት ግፉአን እህቶች የእንቢታቸውን ምንክያት ሲያስረዱ "ለወራት ከቆስንሉ ግቢ ውስጥ ሆነን ጉዳያችን ያልተፈጸመልን ከአይናቸው ርቀን እንረሳለን ! " የሚል ስጋት እንዳላቸው ገልጸውልኛል፡፡ ያም ሆኖ ከቀናት ውዝግብ በኋላ ትናንት ከምሽቱ ሶስት ሰአት ገደማ አምባሳደር መርዋን በድሪ በቆንስሉ ግቢ በመገኘት ጉዳያቸውን እንደሚከታተሉላቸው ቃል ተገብቶችላቸው ሳይዎዱ በግድ "መዲናተል ሃጃጂ !" ወደ ተባለው የሳውዲ መንግስት ለሃጅ ጸሎተኞች ወዳሰራው መጠለያ ተግዘዋል፡፡ ጉዳዩን በቅርብ የሚከታተሉ ወገኖች ተፈናቃይ የኮንትራት ሰራተኞች ወደ ሌላ መጠለያ መሸጋገራቸው  ምክንያት " እርምጃው ችግረኞችን ለመርዳት ሳይሆን ከባልስልጣናትና ለቪዛና ለተለያዩ ጉዳዮች የሚጎርፈው ሰው እንዳያያቸው ለመድረግ ነው ! " ሲጠቁሙ " ከቆንስል መስሪያ ቤቱ መራቃቸው ድሮም ትኩረት ያልሰጡት ሃላፊዎች ጉዳዩ እንዲዘነጋ ያደርገዋል ፡፡ ትኩረት በመስጠት እንዳይከታተሉት ያደርጋል !" በማለት ስጋታቸውን በመግለጽ ላይ ናቸው፡፡ የኮሚኒቲው ሃላፊዎችና አንዳንድ ወገኖች በበኩላቸው የቆንስል ሃላፊዎች ለወሰዱት እርምጃ ድጋፋቸውን ከመስጠት አልፈው እህቶች የቆንስል መስሪያ ቤቱን እርምጃ በአዎንታ እንዲቀበሉት ያግባቡት ፍሬ አግኝቶላቸዋል፡፡ በማህበረሰቡ ስም የተሰየመው የጅዳ ኮሚኒቲ ዛሬ እየሰራው ያለው ስራ በቅንነት ከሆነ ምስጋና የሚቸረው ቢሆንም ኮሚኒቲው አቅም እያጠረው እያደር መዝቀጡ ትናንትም ሆነ ዛሬ መነጋገሪያ ከመሆን አላለፈም፡፡ ከድክመቱ መነሻና መድረሻው ብዙ ቢሆንም ትምህርት ቤቱና ካፍቴሪያውን ማስተዳደር ተስኖት የሚንከላወሰው የጅዳ ኮሚኒቲ በዜጎች ላይ የሚደርሰው አደጋ እየከፋ ሲሄድ ለችግሩ መፍትሄ ለማፈላለግ ህዝባዊ ስብሰባ ጠርቶ ህዝቡን አለማዎያየቱ ማናችንንም ግራ እንዳጋባ ቀጥሏል፡፡ ይህው ኮሚኒዪ በያዝነው ሳምንት  "የኮሚኒቲው የጡት አባት!" በአሽሟጣጮች የሚሸነቆጠውን የቀድሞውን የኮሚኒቲ ስራ አስፈጻሚ አባላት ጠርቶ ባደረገው ውይይትም ከመንግስት ጋር በመሆን ወደ መጠለያ የሚመጡትን እህቶች ለመርዳትና ለኮሚኒቲው ደጎስ ያለ ጥቅም የሚያስገኝ ትላልቅ ፕሮጀክቶችን መቅረጹን ይፋ ሲያደርግ በ"ኮሚኒቲው የጡት አባት!" የሰላ ሂስ ቀርቦበታል ሲሊ ምንጮቸ ገልጸውልኛል፡፡ በማህበረሰቡ ስም የተደራጀው ኮሚኒቲ በተዘበራረቀ መንገድ እንዲህ ይጓዛል . . . ነዋሪው የሚይዝ የሚጨብጠው አጥቷል፤ የክንትራት ቪዛው ያላሰቡለትን ወረት ያዝገኘላቸው ወገኖች ከበር የሚሰራው ሁሉ ትክክል ነው ሲሉ ይሞግታሉ፤ የመንግስት ሃላፊዎች በሚጸድቀው ቪዛ ልክ ለአባይ ገቢ ማሰባሰቡ ተሳክቶላቸዋል፤ በኮንትራት ስራ የሚመጡት ዜጎች ቁጥር ከቀን ወደ ቀን እያደገ መጥቷል ! የሚገፉ የሚበደሉት ወገኖችም ሮሮ ከቀን ወደ ቀን እያየለ መጥቷል ! ግመሏ ትጓዛለች ፤ ውሾቹም ይጮሃሉ . . . አይን ያለው ይመልከት ፤ ጀሮ ያለው  ይስማ ፤ እዝነ-ልቦና ያለው ራሱን ይጠይቅ !